ሥራ አጣን ወይስ ስራው አጣን?
በፍቅርተ ተሾመ
ሜሮን አልጋዋ ላይ ተኝታለች፡፡ እንደ ወትሮዋ ሁሉ ሌሊቱን ሙሉ ፊልም ስታይ አድራ ቀትር ላይ ነው የነቃችው፡፡ ከመንቃቷ ሀሳቦች ሁሉ እኔ ልቅደም ይሸቀዳደማል፡፡ ቤተሰቦቼ ምን ያስቡ ይሆን፣ እኔስ ግን መቼ ነው ሁሌ አንድ አይነት የሚሰለች ኑሮ የምኖረው፣ ቤተሰቦቼ አርጅተዋል ይሄ ሁሉ ለፍተውብኝ ሳልክሳቸው ጊዜው ሄደኮ እያለች ታብሰነስናለች፡፡
አንድ ግለሰብ በህይወት ሂደቱ ውስጥ ቤተሰብ፣ ጎረቤቶቹ እና በትምህርት ቤት አካባቢ ያሉ ሰዎች ማንነቱ ላይ ቀጥተኛ ተፅእኖ ኖሯቸው ይገነቡታል ደግሞም በተዘዋዋሪ ሲወለድ ካዋለደው/ችው ነርስ ወይ ዶክተር አንስቶ የልደት ካርዱን አትሞ፣ ፈርሞ እስከሚሰጠው ሰው ድረስ የህይወቱን ማይክሮ ሰከንዶችም ቢሆን ጊዜ ይወስዳሉ ተፅዕኖም ይኖራቸዋል ተብሎ ይታሰባል፡፡ በዚህም የአንዳችን ከአንዳችን ጋር ያለንን ባህላዊ፣ ማህበራዊ እና ስነልቦናዊ ትስስር መፍታት እና መበተን አስቸጋሪ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ሂደት ሰው እያደገ ከልጅነት ወደ ወጣትነት ይደርሳል የተሰጠውን ለመስጠት ደግሞ በድጋሚ ለመቀበልም ዝግጅት ወደ ማድረግ ይደርሳል፡፡ በተፈጥሮም ጉልበት፣ ሃይል፣ ፍጥነት፣ ክህሎትን በሰፊው እንድንጠቀምበትና እንድንጠቅምበት ሜዳው ሰፊ ይሆናል፡፡ በሀገራችን 43% የሚሆነውን የህዝብ ቁጥር ድርሻ የሚወስዱት ወጣቶች ናቸው፡፡ እንደ አንድ ሀገር ሀብትነት ደግሞ የሀገሪቷ ምጣኔ ሀብት አንቀሳቃሽ መሆናቸውም የታመነ ነው፡፡ እነዚህ ወጣቶች ደግመሞ ሀገሪቷ ውስጥ ከሚወስዱት ድርሻ ጋር ተያይዞ ያለባቸውም ሀላፊነት አለ፡፡
 ሜሮን በሆቴል እና ቱሪዝም ከኮሌጅ ከተመረቀች አመት ከአራት ወር ሆኗታል፡፡ ስራ ለማግኘት በሰዎች አስፈልጋለች ጋዜጦችን አንዳንዴ ለማየት ትሞክራለች ግን “እኔ የምፈልገው ስራ ማስታወቂያ አይወጣበትም መሰለኝ አያጋጥመኝም” ትላለች፡፡ አለም አንድ ልትሆን ነው በሚባልበት በዚህ ወቅት እንዴት ነው እየተማርን ያለነው የሚለው ትልቅ ጥያቄ ይፈጥራል፡፡ አንድ ኢትዮጵያዊ ወጣት አለም አቀፋዊ አስተሳሰብ ይዟል ወይ፤ የተማረው ትምህርት የቀጣሪውን ፍላጎት ያሟላል ወይ የሚሉት ጥያቄዎች መልስ የሚያሻቸው ጉዳዮች ናቸው፡፡ደግሞም መማር ብቻ ሳይሆን ብቁ መሆንም በራሱ፡፡ ምክንያቱም ሀገሪቱ ልማት እያስቀደመች በመሆኑ እና ይሄም ደግሞ መንገዱ ኢንቨስተሮችን የሚጠራ ነው የሚሉት በዩኒቲ ዩኒቨርስቲ መምህር የሆኑት አቶ ፋሲል፤ ታዲያ እነሱ ይዘው የሚመጡበት የራሳቸው መንገድ ሲኖራቸው እኛ ደግሞ እንዴት ነው ራሳችንን ይዘን የምንቀላቀለው ሌላው ጥያቄ ነው ለዚህም አሁን የተጀመረው አንዱ መንገድ በአፍሪካ ህዳሴ ማዕቀፍ ውስጥ ያለው የኢትዮጵያ ህዳሴ ነው ይህ ማለት አለም አቀፋዊ ተፈጥሮ ያለው፤ የራሳችንን ማንነት፣ ለዛ፣ ጥበብ እና መንገድ ይዘን ማደግን ነው የሚያቀነቅነው፡፡ ለምሳሌ የራሳችን የጊዜ ቀመር አለን ይህንን ይዘን አለምአቀፋዊ ምህዳር ውስጥ ብንገባ እና መዋቅራችን  በእርሱ ላይ መገንባት ማለት ነው፡፡
ሜሮን 26 አመት ሊሆናት ቀናት ቢቀራትም እለት እለት ኑሮዋ መመሳሱሉ እና ማሰልቸቱ ብቻ ሳይሆን ስራ ስለሌላ የገቢ መጠኗም ነፃነት እንደነሳት ትናገራለች፡፡ ‹‹ብዙውን ቀኔን የማሳልፈው እቤት ውስጥ ፊልም እያየሁ ወይ ከቤተሰቦቼ ጋር ነው አንዳንዴ እቤት ሆኜ ጓደኞቼ ደውለው “ከስራ በወጣ እንገናኝ” ሲሉኝ በጣም ይደብረኛል አንደኛው እንደነሱ የምመዘው ብር የለኝም በዛ ላይ እነሱ በስራ መንፈስ ሲግባቡ እኔ በዛ ሰዓት የሚሰማኝ ነገር ደስ አይልም፡፡ አንድ ሰው ስራ አጥ ነው ስንል ገቢ የለው እያልን ነው ስለዚህ ስራ አጥ የሆኑ ሰዎች በበዙ ቁጥር ማህበራዊ ስርዓቱ ይናጋ ወይም መንገዱን ይለቃል፣ የዋጋ ንረት ይፈጠራል፣ የገበያ ስርዓቱ ይፈርሳል፡፡
ስራ አለ የለም
በምጣኔ ሃብት አመክንዮ ስራ አጥነትነትም ሆነ ስራ መጥፋት የማይችሉ ነገሮች ናቸው የምትለው ደግሞ ወ/ሮ ሰምሀር በመቀሌ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ መምህር ስትሆን ሆኖም ግን ስራ አጥነት ቁጥሩን ማሳነስ ይቻላል ይሄ ደግሞ ሊሆን የሚችልባቸው መንገዶች አሉ እነዚህም የምጣኔ ሀብት ባለሞያዎች እንደሚያስቀምጡት ይህን ክፍተት የፈጠሩትን ቀዳዳዎች ቀድሞ ለይቶ በማወቅ ነው፡፡ ከነዚህ ውስጥ የኛን ሀገር ነባዊ ሁኔታ የሚገልፁትን ሰምሀር እንደዚህ ታስቀምጣቸዋለች፡፡ አንደኛው ስራ ሁሉ አንድ አይነት ባለመሆኑ እና የተለያዩ ችሎታ እና ልምድ ስለሚጠይቅ የተፈለገው ሰው በተፈለገው ሰዓት እና ቦታ ማግኘት አዳጋች ይሆናል ሌላኛው ምክንያት የሰዎች ፍላጎት ላይ ይወድቃል ሰዎች ፍላጎታቸው የሆነውን ስራ በመጠበቅ ሂደት ውስጥ ስራ በማጣት ሊቀመጡ ይችላሉ፡፡
ታዲያ በዚህ ጊዜ ይሄ ሰው የሚፈልገው የስራ አይነት የለም ማለት ሳይሆን የፈላጊ እና ተፈላጊ አለመገናኘት ነው ፡፡ ያለ ስራ የሚቀመጥበት ጊዜ ሊረዝምም ሊያጥርም ይችላል ይሄ የሚወሰነው መረጃውን የሚያገኝበት ወቅት ነው ስለዚህ በሌላ መልኩ የመረጃ ክፍተት በራሱ ሰዎችን ሰራ አጥተው እንዲቀመጡ ያደርጋቸዋል ማለት ነው፡፡
ሜሮን የምትፈልገው እርሷ በተማረችበት የስራ መስክ ብቻ መስራት ነው፡፡ ለምን ተማርኩና ነው ሌላ ስራ የምሰራው የተመርኩት ልሰራበት ነው” ትላለች፡፡
ብንያም 22 አካባቢ በጥቃቅን እና አነስተኛ ተደራጅቶ የሚሰራ ወጣት ሲሆን ወደዚህ የገባሁት በቃ ግድ ሆኖብኝ ነው ይላል የእንጨት ስራ ከሌሎች ጓደኞቹ ጋር ሆኖ እየሰራ ይገኛል፡፡ ብንያም ግን አሁንም ቢሆን በስራው ብዙም ደስተኛ አይደለም፡፡ ትምህርቱን ለመቀጠል ቢያስብም እቤት የምትጠብቀው የአንድ አመት ልጁ እና የሚያስተዳድረው ቤተሰብ ኃላፊነት ነገሮችን አክብዶበታል፡፡ እርሱ እንደሚለው ቢያንስ ይሄንን ስራ ይዤ ከፍ ማለት የበለጠ ዕውቀትን ማግኘት እፈልጋለሁ “ከተፃፈልኝ አይቀር እንግዲ”፡፡ ሌላኛው ትላለች ሰምሀር አንድ ሰው ያለው ችሎታ ካለው የማህበረሰባዊ ፍላጎት አንፃር እያሳደገ ሄዷል ወይ የሚለው በራሱ ትልቁን ክፍተት የሚፈጥር ነገር ነው፡፡ ይሄ ማለት በፊት በታይፒስትነት ይሰራ የነበረ ሰው አሁን ያ አገልግሎት በኮምፒውተር በመተካቱ የኮምፒውተር ክህሎቱን እስኪያሳድግ የሚወስድበት ጊዜ ክፍተቱን ይፈጥራል፡፡
ስለዚህ እነዚህን ክፍተቶች መድፈን የመፍትሔው አንድ አካል ይሆናል ማለት ነው፡፡ አቶ ፋሲል ስለዚህ ሲያስረዱ በስራ ዘርፎች ውስጥ የሚታዩትን ክፍተቶች መፈለግ እና በነዚህም ቦታዎች ላይ ተፈላጊውን ባለሙያ የማስገባት ስራ እንዲሁም ይሄን ማዋሀድ እና ማጣጣም የሚሆነው የምኒስቴር መስሪያ ቤቶች እንደሆነ ይገልፃሉ፡፡ በተለይም ሰፊ ክፍተት የሚታይበት የኢንዱስትሪው፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ ደግሞ የተማሩም ያልተማሩም ብዙ ወጣቶች በጥቃቅን እና አነስተኛ በመደራጀት ስራዎችን መስራታቸው እንደ ተሞክሮ ዘወትር ብዙ ሲነገርለት የሚሰማ እና የሚታይ ነው፡፡ 86% የሚሆነው የገጠር ቤተሰብ ስራ አጥ በሆነበት ሀገር ጥቃቅን እና አነስተኛ ሀገሪቷ ልታጣ የነበረውን የነዚህን ሰዎች ፍሬ ታገኛለች ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ትምህርት፣ ችሎታ እና ልምድ ሳይጠይቅ በቀላሉ እራሳቸው ባላቸው አቅም እና ችሎታ ላይ የሚወሰን በመሆኑ እናት ሴቶችን፣ ያልተማሩ የማህበረሰብ ክፍሎችንና ሌሎችን አሳታፊ ስለሚያደርግ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ላይ የተማሩ ሰዎችን በማደራጀት ማለት በተማሩበት መስክ አገልግሎት መስጠት የሚችሉ ሰዎችን በጥቃቅን ማደራጀት ሚዛኑን እንዳይመጣጠን ያደርገዋል ይላሉ፡፡  
አብርሃም በአረብ ሀገር ለ8 አመታት ሲሰራ ቆይቶ ይሰራበት የነበረውን ቀላል እና ውሃ ቆጣሚ መሳሪያ ናሙና ወደ ሀገሩ ይዞ በማምጣት ሀገር ውስጥ ያሉ ይህን መሳሪያ ሊያመርቱ የሚችሉ ድርጅቶች ጋር በመውሰድ ስራውን ለመጀመር ጠቅልሎ የመጣው ከ3 አመት በፊት ነው፡፡ ይቺን አገልግሎቷም ስራውም ቀላል የምትመስለው ስራ ለመጀመር ግን 4 አመታትን ፈጅቶበታል፡፡ “በጣም ፈታኝ እና ተስፋ አስቆራጭ የነበረው ደግሞ የስራ መስኩን ተረድቶ ፍቃድ ለመስጠት የሄድኩበት መንገድ ነው” ይላል፡፡ ከባለቤትነት አንስቶ እስከ ንግድ ፈቃድ መስጠት ምን ብለን እንስጥህ በሚል ከሁለት አመት በላይ እንደለፋ ይናገራል፡፡    
ስራ አጥነትን ለመቀነስ ሌላኛው መንገድ ስራ ፈጠራ ነው፡፡ ይሄ ዘርፍ ገና ያልተነካ ነው የሚሉት አቶ ፋሲል ስራ ፈጠራ ሲባል የአንድ ሌሊት ዕቅድና ወጤት አይደለም የሌሎች ሀገሮችን ልምድ ለማየት ብንሞክር እንኳን አስር እና አስራ አምስት አመት ይፈጃል፡፡ አንድ ስራ ፈጣሪ በነዚህ ሀገሮች ውስጥ በመጀመሪያ ደረጃ ላይ እያለ ንድፈ ሃሳቡን ማዳበር የሚያስችል የት/ት ስርዓት አለ ከዛም ባለው ሰፊ ጊዜ ደግሞ አስፈላጊውን ቁሶች እና ገንዘብ ያዘጋጃል ከዚህ በኃላ ነው ከመንግስት ጋር በቀጥታ የሚገናኘው እኛ ጋር አሁን የባለቤትነት ማረጋገጫ የሚሰጥ ቢሆንም ከታች ጀምሮ የማሰልጠን ስራ ይጠይቃል እሱም ቢሆን መንገዱ ከባድ ነው ይላሉ፡፡

ስለዚህ አገልግሎት የሚሰጡት አካላት በራሳቸው የተገኘውን አዲስ ሰራ ባለመረዳታቸው ምክንያት ትልቅ ጋሬጣ ይፈጥራሉ፡፡ ሆኖም ግን ስራ ፈጠራ የሀገርን የግብር ስርዓት ከማስኬድ በላይ ሀገሪቷን እውቅና በሰጠችው ስራ መልሳ እውቅናን ታገኝበታለች፡፡ 

Comments

Popular posts from this blog